TIKVAH-ETHIOPIA
1.53M subscribers
59.3K photos
1.51K videos
214 files
4.11K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
ህፃን ልጇን እንደወለደች ጫካ የጣለች ግለሰብ በ2 አመት ፅኑ እስራት እንድትቀጣ ተፈረደባት።

ተከሳሽ ግለሰብ ታህሳስ 13 ቀን 2015 ዓ.ም በጎንደር ከተማ ፤ ፋሲል ክፍለ ከተማ አንቸው ቀበሌ በተለምዶ ፈሲል ከተማ እየተባለ ከሚጠራ አካባቢ በሠላም ወንድ ልጅ መውለድዋን የክስ መዝገቧ ያስረዳል።

ተከሳሽ የእናትነት ኃላፊነት ለመወጣት ያለባትን ግዴታ ወደ ጎን በመተው ከወለደችው በ40 ደቂቃ እድሜ ያለውን ወንድ ልጅ ህፃን በስሚንቶ መያዣ ማዳበሪያ በመጠቅለል ጫካ ውስጥ ትጥላለች።

ህፃኑ ከምሸቱ 1 ስዓት ከ20 ደቂቃ በአካባቢው ነዋሪ በሆነ ግለሰብ ተገኝቶ ጎንደር ዩኒቨርስቲ ህክምና ሳይንስ ኮለጅ በሀኪሞች እንክብካቤ እየተረዳ በመልካም ጤንነት ይገኛል፡፡

ወንጀል የፈፀመችው ግለሰብ የወለደችውን ህፃን ለአደጋ በማጋለጧ ክስ ተመስርቶባታል።

ተከሳሽዋ የመንግስት ጠበቃ እንዲቆምላት ተደርጎ በራሷ ነፃ ፈቃድ ጥፋተኛ መሆኗን አምና የእምነት ቃሏን ሰጥታለች።

የጎንደር ከተማ ወረዳ ፍ/ቤት በእምነቷ መሠረት ጥፈተኛ ብሎ በህግ የተፈቀደላትን ማቅለያ በመያዝ ታህሳስ 25 ቀን 2015 ዓ. ም በዋለው የወንጀል ችሎት በ2 አመት ፅኑ እስራት እንድትቀጣ ተወስኖባታል፡፡

ፍርድ ቤቱ በተከሳሽ የተሠጠው ቅጣት ተመሳሳይ ወንጀል ሠዎች ቢፈፅሙ ከተጠያቂነት ማምለጥ እንደማይቻሉ አስተማሪ መሆኑ ተገልጿል።

ህፃኑን ለወደፊቱ ረጅ ድርጅቶች ወስደው እንዲያሳድጉት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ንግግር መጀመሩ ተገልጿል።

መረጃው የጎንደር ከተማ አስተዳደር አቃቤ ህግ ነው፡፡

Credit : Gondar Communication

@tikvahethiopia
አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ከ4 ዓመታት በኃላ ወደ ሩጫ ውድድር ልትመለስ መሆኑን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዘግቧል።

የ3 ጊዜ የኦሎምፒክ እና የ5 ጊዜ የዓለም ሻምፒዮና አሸናፊዋ አትሌት ጥሩነሸ ዲባባ ከ10 ቀናት በኃላ በሚካሄደው 22ኛው የሂውስተን ግማሽ ማራቶን ትሳተፋለች ተብሏል።

አትሌት ጥሩነሽ በግማሽ ማራቶን 66 ደቂቃ ከ50 ሰከንድ የግሏ ፈጣን ሰዓት አላት።

በሂውስተን ግማሽ ማራቶንም በርቀቱ 67 ደቂቃ ከ11 ሰከንድ ያላት አሜሪካዊቷ ኤምሊ ሲሰን እና 66 ደቂቃ ከ47 ሰከንድ ያላት ኢትዮጵያዊቷ ህይወት ገ/ኪዳን የጥሩነሽ ተፎካካሪዎች ናቸው።

#የኢትዮጵያ_ቴሌቪዥን

@tikvahethiopia
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለ5 የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የመኖሪያ ቤት ማበረከቱ ተሰማ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለ5 የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች በከተማ አስተዳደሩና ባለሃብቶችን በማስተባበር የተገነባ የመኖሪያ ቤት እንዳበረከቱ ኤፍ ቢ ሲ ዘግቧል።

ለኪነጥበብ ባለሞያዎቹ የተበረከተው ካዛንቺስ የልቤ ፋና ትምህርት ቤት አካባቢ ከተገነባ መኖሪያ ቤት መሆኑ ተገልጿል።

ቤት የተበረከተላቸው ፦

- የዜማና ግጥም ደራሲ ይልማ ገብረአብ፣
- ድምፃዊ ጌታቸው ካሳ፣
- ድምፃዊ አሸናፊ ከበደ፣
- ሻምበል በላይነህ እና በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው የሬዲዮና ቴሌቪዥን ድራማ ደራሲው መስፍን ጌታቸው ወላጅ እናት ወይዘሮ ሎሚናት ገብረመስቀል መሆናቸው ተገልጿል።

@tikvahethiopia
' ወጂዝ ሪል ስቴት ' በከፍተኛ የጥራት መመዘኛ እንደገነባቸው የገለፃቸውን 53 የአፓርታማና የንግድ ሱቅ ቤቶችን ለቤት ባለቤቶች ማስረከቡን ገልጿል።

" በሪል ስቴት ዘርፍ በርካታ ስራዎችን እያከናወንኩ ነው " ያለው ወጂዝ ሪል ስቴት ፤ ግንባታቸው የተጠናቀቀላቸውን (የዋና መግቢያ በር ፣ የመስኮት መስታወት እንዲሁም የመጨረሻ የቀለም ቅብ) ብቻ የቀሩት በቤተል አካባቢ የሚገኙ በድምሩ 53 ባለ-ሶስት መኝታ አፖርታማ ቤቶችንና የንግድ ሱቆችን ለደንበኞቹ ማስረከቡን አመልክቷል።

በመኖሪያ አፖርትመንቶቹ ግንባታ ሂደት ወቅት በርካታ ደንበኞች በውል መሠረት በወቅቱ ክፍያቸውን ያለመፈፀምና ክፍያ የሟቀረጥ ክፍተቶች መፍጠራቸው እንዲሁም በኮቪድ ወረርሺኝ ወቅት በተፈጠረው የስራ መቀዛቀዝ የርክክብ ጊዜውን በመጠኑ መዘግየቱ ተመላክቷል።

ሪል ስቴቱ በቅርቡ ግንባታቸው በመጠናቀቅ ላይ በሚገኙ #ሌሎች ሳይቶቹ  ለህጋዊና ውላቸውን በአግባቡ በመፈፀም ላይ ለሚገኙ ደንበኞቹ ቁልፍ የማስረከብ ስራ እንደሚሰራ አሳውቋል።

(ዋልተንጉስ ዘሸገር)

@tikvahethiopia
#መልዕክት

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በዓለ ልደትን አስመልክተው " የእንኳን አደረሳችሁ " መልእክት አስተላልፈዋል።

በመልዕክታቸው የሀገራችንን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ አንስተው አባታዊ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

ቅዱስናታቸው ባስተላለፉት መልዕክት ፥ " ቸርነቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር አምላክ በአሁኑ ጊዜ #በሀገራችን የተከሠተው ችግር በከፊልም ቢሆን ረገብ ብሎ የሰላም ጭላንጭል እንድናይ አድርጎናል " ያሉ ሲሆን " ይህ ሰላም የእግዚአብሔር ስጦታ ነውና #ልንወደው #ልናከብረውና #ልንጠብቀው ይገባል " ብለዋል።

" ሰላም በጠፋ ጊዜ በወገኖቻችን ምን ያህል ጉዳት እንደደረሰ በዓይናችን አይተናል። " ያሉት ቅዱስነታቸው " ይህ ዓይነቱ ክሥተት ሊቆም እንጂ ሊቀጥል አይገባም " ሲሉ አስገንዝበዋል።

የተገኘው የሰላም ጭላንጭል ወደ ፍጹም አስተማማኝ ደረጃ በሙሉነት እንዲያድግ ሁሉም በኃላፊነት እንዲሰራ በአጽንዖት አደራ ብለዋል።

በተከሠተው አለመግባባት በአጠቃላይ በሕዝብ ላይ የደረሰው ስብራት ከባድ በመሆኑ የዓለም ማኅበረሰብ የተቻለውን ድጋፍ ሁሉ በማድረግ ሕዝባችንን እንዲያግዝ  መንግሥትና ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች የተጀመረውን የሰላም ጉዞ እንዳይቀለበስ በከፍተኛ ኃላፊነት እንዲሠሩ ጥሪ አቅርበዋል።

ቅዱስነታቸው ፤ " ኢትዮጵያውያን የሆናችሁ ልጆቻችን በተለመደው የመተጋገዝ ቅዱስ ባህላችን መሠረት እርስ በርስ #በመረዳዳት ይህንን ፈተና እንድናልፈው በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን ከአደራ ጋር እናስተላልፋለን። " ብለዋል።

(የቅዱስነታቸው ሙሉ መልዕክት ከላይ ተያያዟል)

@tikvahethiopia
#እንድታውቁት

ከነገ ታህሳስ 28 ቀን 2015 ጀምሮ በአዲስ አበባ #ጠጥተው በሚያሽከረክሩ አሽከርካሪዎች ላይ ቁጥጥር እንደሚጀመር የአዲስ አበባ ትራፊክ ማኔጅመንት ኤጀንሲ መረጃ ያሳያል።

ይህ ቁጥጥር ለ2 ዓመታት ያህል ተቋርጦ የቆየው  በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ነበር።

@tikvahethiopia
በአዲስ አበባ ዙሪያ እየተካሄደ ካለው ቤት የማፍረስ ዘመቻ ጋር በተያያዘ ቤታቸው የፈረሰባቸው ግለሰቦች ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ ቅሬታ አቅርበው ነበር።

በዚህ መሰረትም የጉባኤው 3 የሰብዓዊ መብቶች ባለሞያዎች እና አንድ ሹፌር ታህሳስ 27 " ዓለም ባንክ " አካባቢ ጥቆማውን ለማጣራት ይሄዳሉ ፤ በፖሊስም ተይዘው ያሉበትን ማወቅ ሳይቻል ከቆየ በኃላ በተደጋጋሚ በተደረገ ጥረት አራቱም ሰራተኞችና የድርጅቱ መኪና ዓለምገና ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው እንደሚገኙ ታውቋል።

በተጨማሪም ፤ ኢሰመጉ ባሉት ባለሙያዎች ላይ የተለያዩ #ጫናዎች፣ $ዛቻ እና #ማስፈራራትን ጨምሮ እየደረሰበት እንደሚገኝ አሳውቋል።

ኢሰመጉ ይህ አይነት ድርጊት ከህግ አግባብ ውጭ የሆነና ጉባኤው የተቋቋመበትን ዓላማ (ለሰብዓዊ መብት መከበር) እንዳያስፈፅም እንቅፋት የሚሆንና ባለሞያዎቹ በነፃነት ተንቀሳቅሰው እንዳይሰሩ ለማድረግና #ለማሸማቀቅ የተደረገ ነው ብሎታል።

መንግስት በኢስመጉ ላይ የተለያየ አይነት #ህገወጥ_እስር እና የተለያዩ ጫናዎችን ከመፈፀም ይቆጠብ ያለው ጉባኤው ፖሊስ ሰራተኞቹን #በአስቸኳይ ከእስር እንዲፈታ አሳስቧል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
አጠቃላይ_40_60_ቤት_ፕሮግራም_አሸናፊዎች_ዝርዝር_xls_min_1.pdf
የ20/80 እና 40/60 ባለዕድለኞች ውል እንዲፈፅሙ ጥሪ ቀረበ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ፤ የ14ኛ ዙር 20/80 እና 3ኛ ዙር 40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም የጋራ መኖሪያ ቤቶች የቤት እድለኞች ማሟላት የሚጠበቅባቸውን ቅድመ ሁኔታዎች በማሟላት ከጥር 1ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ዘወትር በሥራ ሰዓት ባሉት 60 የሥራ ቀናት ውስጥ ባለእድለኛው ወይም ወኪሉ ቀርበው ውል መዋዋል እንደሚጠበቅባቸው አሳስቧል።

ከተማ አስተዳደሩ በ14 ኛ ዙር የ2080 የቤት ልማት ፕሮግራም 18 ሺ 930 ቤቶች፣ በ40/60 ደግሞ 6 ሺ 843 ቤቶች እንዲሁም ተጨማሪ 18 ስቱዲዮ ቤቶች በድምሩ 25 ሺ 791 ቤቶችን እጣ የማውጣት መርሃ ግብር በማካሄዱ የሚዘነጋ አይደለም።

ውል የመዋዋያ ቦታው #መገናኛ በሚገኝው የቦሌ ክፍለ ከተማ ቅጥር ግቢ የአንድ ማእከል አገልግሎት መስጫ ውስጥ መሆኑ ተገልጿል።

ምንጭ፦ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

@tikvahethiopia